ክቡር ዶ/ር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ፣ በቤልጂየምና በኔዘርላንድስ ከሚኖሩ የኮሚኒቲ አመራረች ጋር በወቅታዊ አገራዊ ጉዳዮች ላይ ተወያዩ፣

የኢ.ፌ.ዴ.ሪ የፍትህ ሚኒስቴር ሚኒስትር ክቡር ዶ/ር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ በብራስልስና በአካባቢው ከሚኖሩ የዳያስፖራ አመራሮችና የአውሮፓ ዲፌንድ ኢትዮጵያ አስተባባሪዎች ጋር በወቅታዊ አገራዊ ጉዳዮች ላይ ውይይት አካሂደዋል፡፡ ክቡር ሚኒስትሩ አራት አባላት ያሉትን የልዑካን ቡድን በመምራት ለሥራ ጉዳይ በአሁኑ ወቅት በብራስልስ የሚገኙ ሲሆን፣ ዓርብ ሰኔ 10 ቀን 2014 ዓ.ም. በብራስልስና በአካባቢው ከሚኑሩ የዳያስፖራ አመራሮችና አስተባባሪዎች ጋር በአካል፣ እንዲሁም በኔዘርላንድስ ከሚኖሩ የዳያስፖራ አባላት እና በተለያዩ የአውሮፓ ከተሞች ከሚገኙ የዲፌንድ ኢትዮጵያ አስተባባሪዎች ጋር በዙም ተገናኝተው ተወያይተዋል፡፡
ክቡር ሚኒስትሩ በውይይቱ መግቢያ ላይ ባለፉት ሦስት ዓመታት በተለያዩ አገሮች በሚኖረው የዳያስፐራ ማኅበረሰብ የተደረጉ እንቅስቃሴዎችንና ድጋፎችን በተለይም በኮቪድ 19 መከላከል፣ ለመከላከያ ሠራዊታችንና በሰሜኑ የአገራችን ክፍል በተከሰተው ግጭት ጉዳት ለደረሰባቸው ወገኖቻችን የተደረገውን የገንዘብና የማቴሪያል ድጋፍ፣ እንዲሁም በ#NoMore እንቅስቃሴ፣ በታላቁ ጉዞ ወደ አገርቤትና በዒድ እሰከ ዒድ መርሃ-ግብር የተደረጉ የአድቮኬሲና የፐብሊክ ዲፕሎማሲ እንቅስቃሴዎችን በመዘርዘር በራሳቸውና በመንግሥት ስም ምስጋና አቅርበዋል፡፡
በማስከተልም በወቅታዊ አገራዊ ጉዳዮች ላይ ሊነሱ የሚችሉ ጥያቄዎችና አስተያየቶች ከተሰብሳቢዎቹ እንዲነሱ በጋበዙት መሠረት በአገራችን የሕግ የበላይነትን ለማስከበር እየተደረገ ስላለው እንቅስቃሴና በዚሁ ሂደት የዜጎችን መብት ስለማስከበር፣ በተለያዩ ወንጀሎች ተጠርጥረው በቁጥጥር ሥር የሚገኙ ሰዎች አያያዝን በተመለከተ በአቃቤ ሕግና እና በፖሊስ መካከል ሚዛናዊ መስተጋብር ስለማስፈን፣ የተዛባ የሶሻል ሚዲያ አጠቃቀምን ፈር ለማስያዝ ምን እየተደረገ እንደሆነ፣ በፍትህ ዘርፍ የሚካሄደው የሪፎርም ፕሮግራም በምን ደረጃ ላይ እንደሚገኝ እና ሌሎችም በርካታ ጥያቄወዎችን አንስተዋል፡፡ ለተነሱት ጥያቄዎችና አስተያየቶች ክቡር ሚኒስትሩ ሠፊ ጊዜ በመውሰድ ጥልቅ ማብራሪያዎችን ሰጥተዋል፡፡ በመጨረሻም ክቡር ሚኒስትሩ በዳያስፖራ ማኅበረሰቡ እየተደረገውን የአድቮኬሲና የፐብሊክ ዲፕሎማሲ ሥራ አድንቀው ይኸው ተጠናክሮ እንዲቀጥል አሳስበዋል::