128ኛው የዐድዋ ድል በዓል በዛሬው ዕለት በብራስልስ የኢፌዲሪ ኢምባሴ በደመቀ ሁኔታ ተከበረ

የዐድዋ ድል በዓል “ዐድዋ የጥቁር ህዝቦች ድል” በሚል መሪ ቃል ቤኔሉክስ አገራት የሚኖሩ ኢትዮዽያዊያን፣ትውልደ ኢትዮጵያዊያን እንዲሁም የሚሲዮኑ ባልደረቦች በተገኙበት በደማቅ ስነ ስርዓት ተከብሯል:: በበዓሉ ላይም ክብርት አምባሳደር ሂሩት ዘመነ በዓሉ ለኢትዮዽያዊያን የተለየ ትርጉም ያለው መሆኑን፣የዐድዋ በዓል ለጥቁር ህዝቦች የነፃነት ዓርማ ፋና ወጊ መሆኑን: በዐድዋ ኢትዮጵያዊያን የተጠቀሙበት የጦር ስልትና በአጭር ጊዜ ጦርነቱ መጠናቀቁ ለዘመናዊ የጦር ሳይንስ መማሪያ ሊሆን የሚያስችል እንደሆነና ከሁሉም በላይ ለዐድዋ ድል መገኘት የሁሉም ኢትዮጵያዊ ተሳትፎና የሕብረብሔራዊ አንድነት የተንፀባረቀበት እንደነበረ ገልፀዋል:: አዲሱ ትውልድም የአባቶቹን አደራ ማስቀጠልና የራሱንም አሻራ ማስቀመጥ እንደሚኖርበት አሳስበዋል።

በማስከተልም አምባሳደር ሻሜቦ ፊታሞ ስለ ዐድዋ ታሪካዊ ዳራ በሠፊው ገለፃ አድርገዋል:: በመቀጠል ቤልጂየም በሚገኘዉ በአንትወርፕ ዩኒቨርሲቲ የPhD ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ የሚገኙት አቶ ሽመልስ አየለ ዐድዋ ኢትዬጵያ ገፅታ የቀየረ በሚል መነሻ ከዐድዋ ጦርነት በፊት እና በኃላ በውጭው ዓለም ስለነበራት ገፅታ በማነፃፀር አቅርበዋል:: ድሉ በእርግጥም የጥቁሮች ህዝቦች የነፃነትና የፍትህ ጥያቄን በዓለም ለማስተጋባት ለሚደረገው እንቅስቃሴ መሠረት እንደጣለ ገልፀዋል።

የቤልጂየምና የኔዘርላንድስ ኮሚዩኒቲ አመራር አባላትም በዓሉን አስመልክተው የእንኳን አደረሳችሁ መልዕክትና ንግግር ያደረጉ ሲሆን ፥ በመጨረሻም ለበዓሉ የተዘጋጀውን ዳቦ በመቁረስና ሻማ በመለኮስ እንዲሁም ተጋባዥ እንግዶቹ ቀደም ሲል እየታየ የነበረውን የሥዕል ኤግዚቢሽን እንዲጎበኙ በማድረግ የበዓሉ ፍፃሜ ሆኗል።